Teachers and Education Leaders Development

የአማራ ብሄራዊ ክልል ትምህርት ቢሮ  የመምህራንና የትምህርትቤት አመራረሮች ልማት ዳይሬክቶሬት

መግቢያ

የመምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች  ልማት ዳይሬክቶሬት  ተማሪዎች የሚያነሱትን  ብቃት፣ ተነሳሽነትና ሥነምግባር ባላቸው መምህራን የመማር ፍላጎት መሠረት በማድረግ ውጤታማ የሆነ መምህር እና የትምህርት ቤት አመራር  የማፍራት የግብ ስኬትን ይዞ የተደራጀ ዳይሬክቶሬት  ነው፡፡

የመምህራንና የትምህርት ቤት አመራር ልማት  ዳይሬክቶሬት  በዋናነት የአጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ተማሪዎች ወደ መምህራን ትምህርት ኮሌጆች  ከሚገቡበት የምልመላ ተግባር ጀምሮ በሥልጠናና በስራ ሂደት አልፈው ጡረታ እስከሚወጡበት ድረስ ያሉ የተያያዙና የተቀናጁ፥ ለደንበኛው እሴት የሚጨምሩና ተያያዥነት ያላቸውን ተግባራት አሰባስቦ የያዘ ዳይሬክቶሬት  ነው።

በመሆኑም ዳይሬክቶሬቱ በዕውቀት፣ በክህሎትና በአመለካከት የታነጹ ብቁና ተነሳሽነታቸው የዳበረና ውጤታማ መምህራንን በመፍጠር ተማሪዎች በዕውቀት፣ በክህሎትና በአመለካከት የታነጹ እንዲሆኑ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት   የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ትምህርት ቢሮ በአዋጅ ሲቋቋም ይዞት የተነሳውን በክልሉ በስልጣኔ፣ በልማትና በዲሞክራሲ ባህሉ የላቀ ደረጃ ላይ የደረሰ ህብረተሰብ ተፈጥሮ የማየት ራዕዩን ለማሳካት የድርሻውን በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡

  1. የዳይሬክቶሬቱ ግብና አላማ

የዳይሬክቶሬቱ ግብ 

     በክልሉ በሚገኙ የትምህርት ተቋማት  ለደረጃውየሚመጥን የትምህርት ዝግጅት ያላቸው  ብቁ የሆኑ የትምህርት ቤት አመራርእና መምህራንን  በማዘጋጀት   ብቃት ፣ተነሳሽነት እና መልካም ስነምግባር ያላቸው ተማሪዎችን ማፍራት ፣

የዳይሬክቶሬቱ ዓላማ

  • በየደረጃው ያሉ ት/ቤቶች ለደረጃው ብቁ የሆኑ የት/ቤት አመራር እንዲኖራቸው ተከታታይ የሙያ ማሻሻያ ስልጠናዎችን ተግባራዊ ማድረግ፣
  • የህዝብ አገልጋይነት ስሜትን የተላበሰና ብቃት ያለው ውጤታማ የሁነ መምህርና የትምህርትቤት አመራር  መፈጠር
  • በትምህርት ተቋማት የመልካም አሰተዳደር እንዲሰፍን ማድረፈግ
  • የመምህርነት ሙያ በፍላጎት የሚገባበት እንዲሆንና ብቃት ያላቸው መምህራንን በማፍራት ጥራት ያለው ትምህርት መስጠት፣
  • የመምህራን የትምህርት ዝግጁት የተሟላ ለማደረግ አዲስ እጩ መምህራንን በመመልመል የቅድመ ስራ ላይ ስልጠና መስጠት፣
  • በየደረጃው የሚያስተምሩ መምህራንን አካዳሚያዊና ሙያዊ ብቃት ለማሣደግ ፍላጎትን መሠረት ያደረግ  አጫጭር የሙያ ማሻሻያ የሥራ ላይ ስልጠና መስጠት፣
  1. ዳይሬክቶሬቱ ባለድርሻዎች/ አጋር አካላት (Stakeholders)
  • የፌዴራል ትምህርት ሚኒስቴር
  • የክልሉ መንግስት
  • መምህራን ትምህርት ኮሌጆች
  • የዞን ትምህርት መምሪያዎች
  • የወረዳ ት/ጽ/ቤት
  • ት/ቤቶች
  • መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች
  • ትምህርት ቢሮ
  1. ዳይሬክቶሬቱ ደንበኞች
  • ተማሪዎች
  • ዕጩ መምህራን
  • መምህራን
  • ር/መምህራን
  • ሱፐርቫይዘሮች
  1. ደንበኞች ዳይሬክቶሬቱ የሚፈልጉት የአገልግሎት ዓይነት
    • ለተፈላጊው የትምህርት ደረጃ በእውቀት፣ በክህሎትና በአመለካከት ብቁ የሆኑና ይህንኑ ተፈላጊ እውቀት፣ ክህሎትና አመለካከት ማስረጽ የሚችሉ መምህራንን ማግኘት፣
    • ችግር ፈቺ፣ ተማሪዎችን ያማከለ የማስተማር ዘዴን፣ ተከታታይ ምዘናና  ወቅታዊ ግብረ መልስ መተግበር የሚችሉና ዴሞክራሲያዊ የክፍል አመራር ስርዓትን ተግባራዊ የሚያደርጉ መምህራንን ማግኘት፣
    • ተገቢው ሙያዊ ስነ-ምግባርና አዎንታዊ አመለካከት ያላቸውን ለሙያቸው ቁርጠኛ የሆኑና በራሳቸው የሚተማመኑ ተነሳሽነቱ ያላቸውን መምህራን ማግኘት፣
    • ስለሚያስተምሯቸው ተማሪዎች አካላዊ ማህበራዊና ስሜታዊ እድገት የሚረዱ መምህራንን ማግኘት፣
    • የመማር ማስተማሩን ሂደት ጠንካራ የድጋፍና ክትትል ሥርዓት በመዘርጋት ውጤታማ የሚያደርጉ ብቁ ር/መምህራንን፣ ሱፐርቫይዘሮችንና የማግኘት፣
    • በአካባቢ በሚገኝ ቅርብ ኮሌጅ የመመደብ፣
    • ተከታታይ የሥራ ላይ ሥልጠና የማግኘት፣
    • ለመማር ማስተማር ወሳኝ የሆኑ የትምህርት ግብአቶችን በተሟላ ሁኔታ የማግኘት፣
    • ቀልጣፋና የተመቻቸ አገልግሎት የማግኘት (የምክር፣ የቤተ መፅሐፍት፣ የክፍያ ፣ የIT የቤተ ሙከራ፣ የሣይንስ ቤተ ሙከራ፣ የሬጀስትራር፣ የውሃና የመፀዳጃ ቤት፣ የመብራትና የነፃ ህክምና) የማግኘት፣
    • በየትምህርት አይነቱ በቂ መምህራንን በማግኘት ያለምንም የክፍለ ጊዜ ብክነት ሁልጊዜ መማር፣
    • የተቀላጠፈ የሥራ ላይ ሥምሪትና የደረጃ እድገት እንዲኖር፣

 

  1. የምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች ልማት ዳይሬክቶሬት ተግባራት
  • መምህራንን፣ ር/መምህራንና ሱፐርቫይዘሮችን ማልማት
  • መምህራንን፣ ር/መምህራንና ሱፐርቫይዘሮችን ማስተዳደር

በመምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች ልማት ዳይሬክቶሬት   ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል የፍላጎትና የአቅርቦት መሪ ዕቅድ ዝግጅት፣ የቅድመ ሥራና የሥራ ላይ ስልጠና ፍላጎት ጥናት፣ የስታንዳርድና መመሪያ ዝግጅት፣ የሥልጠና ቅድመ ዝግጅት፣ የሥልጠና ፕሮጀክት ዝግጅት፣ የምልመላ፣ የስልጠናና የክትትልና ድጋፍ፣ የመመሪያ ዝግጅት፣ የቅጥር፣ የምደባ፣ የደረጃ እድገት፣ የዝውውር፣ የስንበት፣ የጡረታ፣ ወደ ሥራ የመመለስ፣ የት/ቤት አመራሮች የዲስፕሊን ጉዳይ፣ የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ጥናት ዋና ዋና ተግባራት የሚከናወኑበት ነው

የፍላጎትና የአቅርቦት መሪ ዕቅድ ዝግጅት፡- በክልሉ ውስጥ የሚስፈልገውን የመርሱ ፍላጎት የተመጣጠነ ለማድረግ ታስቦ የሚከናወን ከ5-10 ዓመታት ያለውን የመርሱ ፍላጎትና አቅርቦት የሚመልስ የረጅም ጊዜ ጥናት ነው፡፡

ስታንዳርድ ዝግጅት፡- በመርሱ የስራ ሂደት ውስጥ የሚከናወኑ ተግባራትን በውጤታማነት ለመፈፀም የሚያስችሉ መስፈርቶችን/መለኪያዎችን የያዘ ሰነድ ለማዘጋጀት የሚከናወን ተግባር ነው።

የመመሪያ ዝግጅት፡- በመርሱ የሥራ ሂደት ውስጥ የሚከናወኑ ተግባራትን በውጤታማነት ለመፈጸም የሚያስችሉ የልዩ ልዩ ተግባራት አሠራርን የሚያሳይና የሚያብራራ ሰነድ ለማዘጋጀት የሚከናወን ተግባር ነው።

የስልጠና ፍላጎት ጥናት፡- የረጅም ጊዜ የመርሱን የፍላጎትና የአቅርቦት ጥናት መሠረት በማድረግ በቀጣይ በክልሉ ውስጥ  መሰማራት የሚገባውን መርሱ ታሳቢ በማድረግ ለቅድመ ሥራና ለሥራ ላይ ስልጠና የሚገባው የሰው ኃይል የሚለይበት ተግባር ከመሆኑ በተጨማሪ የመርሱ የአጫጭር ጊዜ ሥልጠና ፍላጎት የሚለይበት ጥናት ነው፡፡

የሥልጠና ፕሮጀክት ዝግጅት፡- የተለያዩ ሥልጠናዎችን ለመስጠት የሚገልግሉ ግብአቶችን በማሰባሰብ ስልጠናው የት፣ እንዴት፣ በማን፣ በምን ያህል በጀት መከናወን እንዳለበት የሚያመላክት ሰነድ የሚዘጋጅበት ተግባር ነው፡፡

ምልመላ፦ በቅድመ ስራና በስራ ላይ ስልጠና ወደ መምህራን ትምህርት  ተቋማት ገብተው የሚሰለጥኑ መርሱ ለመለየት የሚጠቅም ተግባር ነው።

የሥልጠና ቅድመ ዝግጅት፡- የመጀመሪያ ደረጃ መምህራን ማሰልጠኛ ሥርአተ ትምህርት ክልላዊ ይዘት እንዲኖረው የሚደረግበት፣ ክልላዊ የማሰልጠኛ ሞጁል ለማዘጋጀት የሚረዳ ስታንዳርድ የሚቀረጽበትና ሞጁሎች ተዘጋጅተው ሲጠናቀቁ የሚሠራጩበት እንዲሁም አጫጭርና ወቅታዊ ስልጠናዎችን ለመስጠት የሚያስችል የሥልጠና ሰነድ ዝግጅት የሚከናወንበት ተግባር ነው፡፡

ስልጠና መስጠትና መከታተል፦  በተለየው የመርሱ ሥልጠና ፍላጎት መሰረት ወቅታዊና አጫጭር ስልጠናዎችን የመስጠት ተግባር ነው፡፡

ስልጠና መከታተል፥መደገፍ ፣መገምገምና ግብረመልስ መስጠት

  • ሥልጠና  መከታተልና መደገፍ፡- በሥልጠናው ወቅት የሚያጋጥሙ ችግሮችንና ሥርዓተ ትምህርቱን ለማሻሻል የሚረዱ መረጃዎችን በማሰባሰብ፣ የሚሰጡ የትምህርት ይዘቶችንና መካተት የሚገባቸውን ኮርሶች በየጊዜው በመከለስ የማስተካከል ሥራ በመሥራት ሥልጠናውን ውጤታማ የማድረግ ተግባር ነው፡፡
  • ሥልጠናውን መገምገምና ግብረ መልስ መስጠት፡- የሚሰጡት ሥልጠናዎች በምን ያህል ደረጃ ጥራታቸውን ጠብቀው መሰጠታቸውንና ከሚጠበቀው ግብ አንጻር የተሰጠው ሥልጠና ምን አይነት ለውጥ ማምጣቱን ለማረጋገጥ የሚከናወን ተግባር ነው፡፡

የመምህራን ቅጥር፦ በየደረጃው በተለየው የመርሱ ፍላጎትና አቅርቦት ጥናት መሠረት በየተቋማቱ ያልተሟሉ መርሱን ለማሟላት የሚከናወን ተግባር ሲሆን ተግባሩም በጀት በሚያስተዳድሩ ወረዳዎች/ከተማ አስተዳደሮች ደረጃ የሚከናወን ይሆናል።

የመርሱ ምደባ፦ በተለያየ ምክንያት ከተሿሚነት ተነስተው ወደሴክተሩ ተላኩትን መርሱና ከሱፐርቫዘርነትና ከር/መምህርነት የሚወርዱ መርሱን ባለው ክፍት የሥራ ቦታ ወደ ሥራ የማሰማራት ተግባር ነው፡፡

የመርሱ ዝውውር፦ መርሱ ይሰሩበት ከነበረው ተቋም /ወረዳ/ዞን/ክልል በጥያቂያቸው መሰረት ወደ ሌላ ተቋም /ወረዳ/ዞን/ክልል የሚዛወሩበት ተግባር ነው።

የመርሱየደረጃ እድገት፦ በስራቸው ወይም በአገልግሎት አሰጣጣቸው የሚያገለግሉት ደንበኛ ያረኩ/የተማሪዎቻቸውን ውጤት ያሻሻሉ፤ የሚመሩትን ተቋም የለወጡ ወይም የሚደግፉትን መምህርና ርዕሰ መምህር በመለወጥ ተቋማዊ ውጤት ያስመዘገቡ መርሱ የሙያ ማዕረግ ለውጥ እንዲያገኙና ተነሳሽነታቸው ጐልብቶ ለበለጠ ስራ እንዲተጉ ለማድረግ የሚከናወን ተግባር ነው።

የመርሱ ስንብት፦ መርሱ በራሳቸው ጥያቄ፣ ባልታወቀ ምክንያት ከስራ በመጥፋታቸው ወይም በስነምግባር ችግር ወይም በብቃት ችግር ከስራ የሚወገዱበት ተግባር ነው።

የመርሱ ወደ ስራ መመለስ፦ ባልታወቀ ምክንያትና በራሳቸው ጊዜ ከስራቸው ተለይተው የቆዩ መርሱ የሚያቀርቡት መረጃ አሳማኝ ሆኖ ሲገኝ እና በጀትና ክፍት የስራ ቦታ መኖሩ ሲረጋገጥ መርሱ ወደ ሥራ የሚመለሱበት ተግባር ነው።

የመርሱ ጡረታ፦ መርሱ በመንግስት ህግና ደንብ መሠረት የተፈቀደውን ያህል ካገለገለ ወይም በጤና ችግር ምክንያት ወይም በራስ ጥያቄ ወይም በመስሪያ ቤቱ ፍላጎት ወይም በሞት የተለየ ከሆነ ለሰራተኛውና ሰራተኛው ለሚያስተዳድራቸው ቤተሰቦች የሚሰጥ መብት ሆኖ በመንግስት ህግና ደንብ መሠረት በተቀመጠው አግባብ በመፈጸም የመርሱ ዋስትና እንዲረጋገጥ የሚደረግበት ተግባር ነው።